ታንዛኒያዊው ባሕላዊ ማዕድን አውጪ በአንድ ቀን ሚሊየነር ያደረገውን ማዕድን አገኘ
- GH ETHIO NEWS
- Jun 25, 2020
- 1 min read
ታንዛኒያዊው ባሕላዊ ማዕድን ቆፋሪ አንድ ላይ 15 ኪሎ ግራም የሚመዝኑ ሁለት ግዙፍ ውድ የሆነውን ታንዛናይት ማዕድን በማግኘቱ በአንድ ቀን ሚሊየነር ሆነ።
ሁለቱ የከበሩ የማዕድን ድንጋዮች እስካሁን በቁፋሮ ከተገኙ መካከል ግዙፎቹ ሳይሆኑ እንደማይቀሩ ተገምቷል።
አንዳንድ ምንጮች እንዳሉት እስካሁን የተገኘ ግዙፉ የታንዛናይት ማዕድን የሚመዝነው አራት ኪሎ ግራም የማይሞላ ሲሆን የተገኘውም ከ15 ዓመት በፊት እዚያው ታንዛንያ ውስጥ ነበረ።
በሰሜናዊ ታንዛኒያ ነዋሪ የሆነው ባሕላዊ ማዕድን ቆፋሪ ሳኒኑ ላይዘር በቁፋሮ ያገኛቸው ሁለቱ የከበሩ ድንጋዮች 9.2 እና 5.8 ኪሎ ግራም በመመዘን ነው ክብረወሰኑን በመያዝ ግለሰቡንም ለሚሊየነርነት ያበቁት ተብሏል።
ሳኒኑ እነዚህን የማዕድናት መቼ እንዳገኛቸው የታወቀ ነገር ባይኖርም ነገር ግን ዛሬ ለአገሪቱ መንግሥት የማዕድን ሚኒስቴር በአጠቃላይ በ7.8 ቢሊየን የታንዛንያ ሽልንግ ወይም በ3.43 ሚሊየን ዶላር ሸጧቸዋል።
በሽያጩ ወቅት የአገሪቱ ፕሬዝዳንት ጆን ማጉፉሊ ስልክ ደውለው ሳኒኑ ላይዘርን እንኳን ደስ ያለህ ብለውታል።
ፕሬዝዳንቱ ጨምረውም "ይህ የባሕላዊ ማዕድን አውጪዎች ጥቅም ሲሆን ታንዛኒያም ምንያህል ባለጸጋ መሆኗን የሚያሳይ ነው" ብለዋል።
ማጉፉሊ ወደ ስልጣን በመጡበት ጊዜ አገሪቱ ካላት የማዕድን ሃብት ተጠቃሚ እንደሚያደርጉና ከዘርፉ መንግሥት የሚያገኘው ገቢ ከፍ እንዲል እንደሚጥሩ ቃል ገብተው ነበር።
ከሦስት ዓመት በፊት በዓለም ብቸኛው የታንዛናይት ማዕድን ማውጫ ነው የሚባለውን በሰሜናው የአገሪቱ ክፍል ከኪሊማንጃሮ ተራራ ግርጌ የሚገኘውን አካባቢ በጦር ሠራዊታቸው እንዲጠበቅ አድርገዋል።
ታንዛናይት በምድር ላይ በብዛት ከማይገኙ ውድ ማዕድናት መካከል ሲሆን የፔኒሲልቫንያ ዩኒቨርስቲ በአካባቢው የሚገኝ የማዕድን ጥናት ባለሙያን ጠቅሶ እንዳለው ማዕድኑ በሚቀጥሉት 20 ዓመታት ውስጥ ሊመናመንና ሊያልቅ ይችላል።
Comments