አሜሪካ የደም ፕላዝማ ለኮቪድ-19 በሽተኞች እንዲውል ፈቀደች
- GH ETHIO NEWS
- Aug 24, 2020
- 2 min read
አሜሪካ የደም ፕላዝማን ለኮሮናቫይረስ ታማሚዎች ድንገተኛ ሕክምና እንዲውል ፈቀደች።
የአሜሪካ ምግብና መድሃኃኒት አስተዳደር የደም ፕላዝማ ለኮሮናቫይረስ ታማሚዎች ድንገተኛ ሕክምና እንዲውል ፈቃድ ሰጠ።
አንድ ሰው በኮሮናቫይረስ ሲያዝ የተፈጥሮ በሽታን የመከላከያ ሥርዓቱ በሽታን አምጪ ተህዋስን የመከላከያ ዘዴን ያዘጋጃል፤ ይህም ቫይረሱን በማጥቃት ወደ በሽታ እንዳይሸጋገር ያደርጋል።
ይህ ሂደትም በአንድ ወር ውስጥ የሚፈጠር ሲሆን ፕላዝማ በተባለውና በደም ውስጥ ባለው ፈሳሽ ክፍል ውስጥ የሚገኝ ነው።
ይህንን ፕላዝማ በኮቪድ-19 በጠና ለታመሙ ሰዎች በመስጠት ከቫይረሱ ጋር ፍልሚያ የገጠመውን የእራሳቸውን ተፈጥሯዊ በሽታን የመከላከያ ሥርዓት በማጠናከር ከበሽታው እንዲያገግሙ ለማገዝ የሚያስችል ነው።
በመሆኑም ሕክምናው ከበሽታው ካገገሙ ሰዎች ከተወሰደና በበሽታ መከላከል አቅም [አንቲ ቦዲ] የበለፀገውን ይህን የደም ፕላዝማ ይጠቀማል።
ይህ ሕክምና ቀደም ብሎ በአሜሪካ ከ70 ሺህ በላይ ሰዎች ላይ ጥቅም ላይ ውሏል።
ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕም ሕክምናው 35 በመቶ ሞት ሊቀንስ እንደሚችል ተናግረዋል።
ሕክምናው ጥቅም ላይ እንዲውል የተፈቀደው ፕሬዚደንት ትራምፕ የምግብና መድሃኒት አስተዳደሩን የክትባት የመገኘት ሂደቱን እና ሕክምናውን ለፖለቲካ ፍጆታ አውሎታል ሲሉ ከከሰሱ ከአንድ ቀን በኋላ ነው።

ይህ ውሳኔ የተገለፀውም ትራምፕ በዋይት ሃውስ ለሚኖራቸው ቆይታ በሁለተኛ የምርጫ ዘመን ለማሸነፍ ዘመቻቸውን በሚያስተዋውቁበት የሪብሊካን ብሔራዊ ስብሰባ ዋዜማ ላይ ነው።
ፕሬዚደንቱ "ለረዥም ጊዜ ስፈልገው የነበረው ነው የሆነው። ከ'ቻይና ቫይረስ' ጋር እየታገልን ባለንበት በአሁኑ ጊዜ የበርካታ ሰዎችን ሕይወት ለመታደግ ይህንን የምስራች ሳበስር እጅግ ደስ እያለኝ ነው" ሲሉ እሁድ ዕለት ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።
ፕሬዚደንት ትራምፕ ኮሮናቫይረስ ከቻይና ቤተ ሙከራ የወጣ ነው ሲሉ ይወቅሳሉ። ለዚህም ነው 'የቻይና ቫይረስ' እያሉ የሚጠሩት።
የዚህም ሕክምና ሂደትም "ወሳኝ ነው" ሲሉ የገለፁት ፕሬዚደንቱ፤ ከበሽታው ያገገሙ አሜሪካዊያን የደም ፕላዝማቸውን እንዲለግሱ ጥሪ አቅርበዋል።
የምግብና መድሃኒት አስተዳደሩ የደም ፕላዝማ ሕሙማን በበሽታው ተይዘው ሆስፒታል በገቡ በመጀመሪያዎቹ ሦስት ቀናት በትክክል መሰጠት ከቻለ የመሞት እድልን በመቀነስና የታማሚውን ጤና እንደሚያሻሽል ቀደም ብለው የወጡ ጥናቶች እንዳመለከቱ በመጥቀስ፤ ሕክምናው ለመደበኛ ሕክምና እንዲውል ሳይሆን ለድንገተኛ ሕክምና ብቻ እንዲውል ነው ፈቃድ የሰጠው።
ሆኖም ውጤታማነቱን ለመመርመር በርካታ ሙከራዎች ያስፈልጋሉ ተብሏል።
ኤጀንሲው አክሎም በቅርብ ወራት የተሰበሰቡ መረጃዎችን ከመረመረ በኋላ ሕክምናው ጉዳት እንደሌለው ማረጋገጥ እንደቻለ አስታውሶ፤ ሕክምናው ከሚያስከትለው ጉዳት ጥቅሙ ይልቃል ብሏል በመግለጫው።
Comments