ኮሮናቫይረስ በሁለት ዓመታት ውስጥ ሊጠፋ ይችላል'' ደ/ር ቴድሮስ አድሃኖም
- GH ETHIO NEWS
- Aug 22, 2020
- 1 min read
ዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሊጠፋ እንደሚችል ገለጹ።
ትላንት በሲዊዘርላንድ ጄኔቫ ባደረጉት ንግግር ዳይሬክተሩ ስፓኒሽ ፍሉ በጎርጎሮሳውያኑ 1918 በተከሰተበት ወቅት ለመጥፋት የወሰደበት ጊዜ ሁለት ዓመት ነበር ብለዋል።
ዳይሬክተሩ አክለውም ዓለም አሁን ከደረሰችበት የቴክኖሎጂ መራቀቅና ከፍተኛ ምርምሮች አንጻር የኮሮረናቫይረስ ወረርሽኝ ከሁለት ዓመት ባነሰ ጊዜ ውስጥ ሊጠፋ እንደሚችል ገልጸዋል።

''በሌላ በኩል ደግሞ አሁን ባለው ከፍተኛ የሰዎች ማህበራዊ ትስስር ምክንያት የቫይረሱ ስርጭት ከፍተኛ ሊሆንም ይችላል'' ብለዋል ዶ/ር ቴድሮስ።
''ነገር ግን የሰው ልጅ የደረሰበት የቴክኖሎጂ ርቀት ቫይረሱን ለማስቆም የሚረዳ እውቀት በቶሎ እንዲያዳብር ይረዳዋል'' ካሉ በኋላ አሁንም ቢሆንም ግን ብሄራዊ አንድነትና ዓለማቀፍ ትብብር ላይ ከፍተኛ አጽንኦት ሰጥተው አልፈዋል።
የ1918ቱ ስፓኒሽ ፍሉ ቢያንስ 50 ሚሊየን ሰዎችን የገደለ ሲሆን ከኮቪድ-19 ጋር በተያያዘ ህይወታቸውን ያጡ ሰዎችን ቁጥር 800 ሺህ ነው። በአጠቃላይ ደግሞ 22.7 ሚሊየን ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።
ዶክተር ቴዎድሮስ በመግለጫቸው ላይ የግል መከላከያ መሳሪያዎች ወይም 'ፒፒኢ' ስርጭት በተመለከተ ሙስና እየተስተዋለ እንደሆነ ለቀረበላቸውም ጥያቄ መልስ ሲሰጡ ጉዳዩን ''ወንጀል'' ነው በማለት ገልጸውታል።
''ማንኛውም አይነት ሙስና ተቀባይነት የለውም'' ብለዋል።
''ነገር ግን ከፒፒኢ ጋር የተያያዘ ሙስና ለእኔ በግሌ እንደ ነብስ ማጥፋት ነው የምቆጥረው። ምክንያቱም የጤና ባለሙያዎች ፒፒኢ የማያገኙ ከሆነ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ እየጣልን ነው። በተጨማሪም የሚያገለግሏቸው ሰዎችን ሕይወትም ነው ስጋት ውስጥ የምንከተው'' ብለዋል።
Comentários